በመንፈስ ቅዱስ የተሞላ ቤተሰብ

  • ሕፃኑም ዮሐንስ በጌታ ፊት ታላቅ ይሆናልና፥ የወይን ጠጅና የሚያሰክር መጠጥ አይጠጣም፤ ገናም በእናቱ ማኅፀን ሳለ መንፈስ ቅዱስ ይሞላበታል። (ሉቃ ፩፥፲፭)
  • ኤልሳቤጥም የማርያምን ሰላምታ በሰማች ጊዜ ፅንሱ በማኅፀንዋ ውስጥ ዘለለ፤ በኤልሳቤጥም መንፈስ ቅዱስ ሞላባት። (ሉቃ ፩፥፵፩)
  • አባቱ ዘካርያስም መንፈስ ቅዱስ ሞላበትና ትንቢት ተናገረ። (ሉቃ ፩፥፷፯)  

ጽሐፍ ቅዱስ የዚህን ታላቅ ቤተሰብ ታሪክ በሉቃስ ወንጌል ላይ ካህኑ ዘካርያስ እና ከካህኑ ከአሮን ወገን የሆነች ኤልሳቤጥ ሁለቱም በጌታ ትእዛዝና ሕግጋት ሁሉ ያለ ነቀፋ እየሄዱ በእግዚአብሔር ፊት ጻድቃን ነበሩ በማለት ይገልፃል። የመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ የልደት ታሪክም እንዲህ በሚለው በቅዱስ ገብርኤል ብሥራት ይጀምራል፦ ዘካርያስ ሆይ፥ ጸሎትህ ተሰምቶልሃልና አትፍራ ሚስትህ ኤልሳቤጥም ወንድ ልጅ ትወልድልሃለች፥ ሙንም ዮሐንስ ትለዋለህ። ደስታና ተድላም ይሆንልሃል፥ በመወለዱም ብዙዎች ደስ ይላቸዋል። በጌታ ፊት ታላቅ ይሆናልና፥ የወይን ጠጅና የሚያሰክር መጠጥ አይጠጣም፤ ገናም በእናቱ ማኅፀን ሳለ መንፈስ ቅዱስ ይሞላበታል፤ ከእስራኤልም ልጆች ብዙዎችን ወደ ጌታ ወደ አምላካቸው ይመልሳል። እርሱም የተዘጋጁትን ሕዝብ ለጌታ እንዲያሰናዳ፥ የአባቶችን ልብ ወደ ልጆች የማይታዘዙትንም ወደ ጻድቃን ጥበብ ይመልስ ዘንድ በኤልያስ መንፈስና ኃይል በፊቱ ይሄዳል። (ሉቃ ፩፥፲፭-፲፯)

የእግዚአብሔርን ትእዛዝና ሕግጋት እየጠበቀ በቅድስና ይኖር የነበረው ካህኑ ዘካርያስ ከእግዚአብሔር ተልኮ የመጣውን የቅዱስ ገብርኤል ቃል ባለመስማቱ ሕፃኑ እስከሚወለድ ድረስ ድዳ እንደሚሆን በአብሳሪው መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ተነገረው። ይወለዳል የተባለው መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስን የኤልሳቤጥ መፅነስ በቤተሰቡ መካከል ለረጅም ጊዜ ይፈለግ የነበረ ስለነበር ደስታ ሲፈጥር የካህኑ ዘካርያስ ድዳ መሆን ደግሞ ቤተሰቡን የሚያስጨንቅ ሌላ ክስተት ሆነ። ቅድስት ኤልሳቤጥም ባለመውለዷ ምክንያት በአካባቢው ሰዎች ግን እግዚአብሔር እንዳዘነባትና ልጅ እንደከለከላት ይነገርባት ስለነበር የልምላሜዋ ዘመን ካለፈ በኋላ መፅነስ በመቻሏ ነቀፌታዬን ከሰው መካከል ያስወግድልኝ ዘንድ ጌታ በተመለከተበት ወራት እንዲህ አድርጎልኛል (ሉቃ ፩፥፳፭) በማለት ደስታዋን ገልፃለች።

አስቀድሞ በነቢዩ በኢሳይያስ የአዋጅ ነጋሪ ቃል ተብሎ እንደተነገረው የእግዚአብሔርን መንገድ በምድረ በዳ ጥረጉ፥ ለአምላካችንም ጐዳና በበረሀ አስተካክሉ በማለት ፊት አውራሪ ሆኖ የሚላከውን ቅዱስ ዮሐንስን የፀነሰችው ቅድስት ኤልሳቤጥ በፀነሰች በስድስተኛው ወር እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ልትጠይቃት ወደ እርሷ በሔደች ጊዜ እጅግ የሚያስገርም ሁኔታ ተፈጠረ። ይኸውም  ቅዱስ ዮሐንስ በማኅፀን ውስጥ ኾኖ ለቅድስት ድንግል ማርያም እና በማኅፀኗ ላለው ለዓለም መድኃኒት ለኢየሱስ ክርስቶስ ሰግዷል (ሉቃ. ፩፥፳፮-፵፩)

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በየዓመቱ ሐምሌ ፭ ቀን ጴጥሮስ ወጳውሎስ በማለት ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ እና ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ መልካሙን የክርስትና ገድል ተጋድለው ሰማዕትነት የተቀበሉበትን ቀን በታላቅና በተለየ ሁኔታ ታከብራለች። ክርስትናን በማስፋፋት ከፍተኛውን ሚና የተጫወቱት እነዚህ ቅዱሳን አባቶች በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ መልእክታትን ጽፈዋል። ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ ስምንት ምዕራፎችን የያዘ ሁለት መልእክታትን ሲጽፍ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ አንድ መቶ ምዕራፎችን የያዘ አሥራ-አራት መልእክታትን ጽፏል። ለአግልግሎት የጠራቸውም የክብር ባለቤት የሆነው አምላካችን ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።