እግዚአብሔር አምላክ መላእክትን እና የሰውን ልጆች ስሙን እንዲቀድሱ ክብሩን እንዲወርሱ ፈጥሯቸዋል። ለዚህም ቅዱስ ዳዊት ዘይሬስዮሙ ለመላእክቲሁ መንፈስ ወለክለ ይትለአክዎ ነደ እሳት” እንዲል (ዕብ. ፩፡፯)። ፈጥሯቸውም በሦስት ከተሞች በኢዮር፣ በራማ እና በኤረር አሰፈራቸው።

በኢዮር አርባውን ነገድ በማስፈር ለአራት ከፍሎ አጋእዝትን ኪሩቤልን ሱራፌልንና ኃይላትን አድርጓል፤ የኃይላትን አለቃ ቅዱስ ሚካኤልን ሾሞታል “ሚካኤል ሥዩም በዲበ ኃይላት” እንዲል ኋላም በአጋእዝት ላይ አለቃ የነበረው ሰማልያል ሲወድቅ ቅዱስ ሚካኤል በአጋእዝት ላይ ሥልጣን ተቀዳጅቷል። “አሁን የእግዚአብሔር ሠራዊት አለቃ ሆኜ መጥቻለሁ” እንዲል። (ኢያ. ፭፡፲፬)የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል ስልጣኑ አለቅነቱ በእግዚ አብሔር ሠራዊት ሁሉ ላይ ታዳጊነቱ እርዳታውም ለሁሉም ፍጡር ነው። ይኸው እንደ እንግዳ ደራሽ እንደ ጎርፍ ፈሳሽ ሳይሆን የሕይወት መመሪያችን በሆነው በመጽሐፍ ቅዱስ ዘፍ. ፵፰፡፲፮ ላይ እናገኘዋለን። ከክፉ ነገር ሁሉ ያዳነኝ መልአክ እነዚህን ብላቴኖች ይባርክ” (ዘፍ. ፳፰፡፲፪) በማለት እንደተጻፈው በምድረ ሎዛ የመላእክትን የሰው ልጅ ልመና ወደ እግዚአብሔር ሲያደርሱ የእግዚአብሔርን ምሕረት ወደ ሰው ልጆች ሲያመጡ በመሰላል አምሳል ከፍቶ ትድግናቸውን አስቀምጦልናል። የእግዚአብሔርን ቃል ኪዳን እንዲይዙ የአብርሃምን የይስሐቅን የያዕቆብን የሃይማኖት መሪነት አደራ እንዲሸከሙ ለቀጣዩም ትውልድ እንዲያሸጋግሩ ሁለቱን የልጅ ልጆቹን ምናሴንና ኤፍሬምን ለኔ ይሁኑ ሌሎቹ ግን ላንተ ይሁኑ ካለ በኋላ በአመስቅሎ እድ የአባትነቱን ቡራኬ ከሰጠ በኋላ “ከክፉ ነገር ሁሉ ያዳነኝ መልአክ እነዚህን ብላቴኖች ይባርክ” በማለት የአባቶችን አደራ ለመረከብ የቅዱሳን መላእክት ጥበቃ እንደሚያስፈልግና በሕይወታችን በኑሮአችን ውስጥ ዕለት ዕለት መሆናቸውን የእግዚአብሔር ቃል ያስረዳናል።

ነብየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊትም ሰይጣን እሥራኤልን እንዲቆጥር ባነሳሳው ጊዜ በዐውደ አርና ኢያቡሳዊት ዓይኑን አነሣ የእግዚአብሔር መልአክም በምድርና በሰማይ መካከል ቆሞ  የተመዘዘ ሰይፉንም በእጁ ሆኖ ባየ ጊዜ በፊቱ በመስገድ መቅሰፍቱን እንዲያርቁ ለምኖታል፤ በዚያም መሥዋዕት አቅርቦ ተቀባይነት እንዳገኘ በአንደኛ ዜና ፳፩፡፲፮ ተጽፎ እናገኛለን።

እንዲሁም “በእውነት መጽሐፍ የተጻፈውን እነግርሃለሁ በዚህ ነገር ከአለቃችሁ ከሚካኤል በቀር የሚረዳኝ የለም” (ዳን. ፲፡፳፩)። ታላቁ ነብይ ዳንኤል በእውነት ጽሑፉ የተጻፈውን እነግርሃለሁ በማለት የመጋቤ ብሉይ ተራዳኢ ቅዱስ ሚካኤል መሆኑን በማያሻማ መልኩ አስቀምጦልናል።

ወበእንተ ዝ ተገብረ ሎቱ በዓል ስለክብሩና ስለ አማላጅነቱ ወር በባተ በየአሥራ ሁለት ቀን መታሰቢያውን እንድናደርግ አዘዙን ከምን አግኝተው ቢሉ በመጽሐፈ መሳፍንት ፲፫፡፲፯-፲፱ እንዲህ የሚል ኃይለ ቃል እናገኛለን “ የእግዚአብሔር መልአክም ተአምር አደረገ ማኑሄም መልአኩን የነገረህን በደረሰ ጊዜ እንድናከብርህ ስምህ ማን ይባላል ለምንት ትሴአል ስምየ ወመድምም ውእቱ”  ብሎታል ማኑሄም የፍየል ጠቦት ወስዶ ለመሥዋዕት አቀረበ

የእግዚአብሔር መልአክ ከመሠዊያው ነበልባል ጋር ወደ ሰማይ አረገ። ስሜም ድንቅ ነው “ ሚካኤል ብሂል ዕፁብ ነገር” እንዲል ደራሲ። በመሆኑም ዛሬም ለኛ በሚያደርግልን ተአምራት እናከብረዋለን ስእለታችን ሲደርስ ለቅዱስ ሚካኤል ነግሬው ነበረ ብለን ነገራችን በደረሰልን ጊዜ ስሙን እናነሳለን።

የቅዱስ ሚካኤል መታሰቢያኅዳር 12 እና ሰኔ 12 በታላቅ ድምቀት የሚከበርበት ነው። የሰኔ 12 ቀን የሚከበርበት ምክንያት አባ እለ እስክንድሮስ የተባለ አባት ሊቀ ጳጳሳት በሆነበት ወራት የግብፅ ንጉስ የበጥሊሞስ ልጅ ዙሐል የሚባል የኮከብ ጣዖት ሠራች “ወኮነ በውእቱ ምኩራብ ጣዖት ዘብርት” እንዲል በጣም ታላቅና በአውራጃው የገነነ ከ300 ዓመት በላይ የቆየ ወገብሩ ሎቱ በዓል አመ 12 ለወርኃ ሰኔ በዚያም አባ እለእስክንድሮስ ያንን የጣዖት ምኩራብ ወደ ቤተ ክርስቲያን በመቀየር ማኑሄ መሥዋዕቱን ለእግዚአብሔር እንዳቀረበ ለጣዖት ይሠዋ የነበረ መሥዋዕት ለእግዚአብሔር እንዲሆን በማድረግ የሊቀ መልአክት የቅዱስ ሚካኤልን ታቦት አስገብቶ ቅዳሴ ቤቱን አክብረውበታል። ወተሠረዓ ዝንቱ በዓል እስከ ዛቲ ዕለት ይህ በዓል ሆኖ እስከ ዛሬ ተወሰነ።

በዚህች ቤተ ክርስቲያን በየወሩ የቅዱስ ሚካኤል ዝክር የሚያዘክሩ መታሰቢያውን የሚያደርጉ ወፈድፈደሰ በኅዳር ወበሰኔ ባልና ሚስት ነበሩ በጎረቤቱም ይህን ሥራቸውን የማይወድ ሀብታም ይኖር ነበር። ይህም በጎ ሰው ከብዙ ጊዜ በኋላ አረፈ ሚስቱም ፀንሳ ነበር በቅዱስ ሚካኤል አማላጅነት መልኩ በጣም ያማረ ልጅ ወለደች ቅዱስ ሚካኤል ሕፃኑን ባረከው እና የዚህን ንፉግ ባለፀጋ ሀብት እንዲወርስ አዝዟል ብሎ ሲናገር ያደምጥ ነበር። መልአኩን የተናገረውን ሰምቶ ሕፃኑ  አሥር ዓመት ሲሞላው በሳጥን አድርጎ ወደ ባሕር ወርውሮታል በሊቀ መልአኩ ታዳጊነት እሩቅ ሀገር አንድ በግ እረኛ አግኝቶት ስሙን ባሕራን ብሎ አሳድጎታል። ዮናስ በዓሣ ነባሪ ሆድ ሦስት ቀን ያሳደረ አምላክ ይህንንም ባሕራንን ከክፉ ነገር ሁሉ ጠብቆ ከዚያ አድርሶታልና ኋላም ይኸው ባለፀጋ ከነባሕራን ቤት በእንግድነት አድሮ የባሕራንን የስሙን ትርጉም ወራቱን ዓመታቱን ጠይቆ እሱ ወደ ባሕር የወረወረው መሆኑን በመረዳቱ ደብዳቤ በመጻፍ እንዲገድሉት “ቅትሎ ወግድፎ ውስተ ግብ” ብሎ ሰጥቶት ይህቺን የሞት ደብዳቤ ሊቀ መልአክ ለነማኑሄ በሰው አምሳል እንደተገለጠው ለባህራንም በንጉሥ ስፍራ አምሳል ተገልጦ ወደ ሕይወት ቀይሮለታል “እስመ አነ ወሀብክዎ ኮሎ ንዋይየ” በቤት ያለኝን ሁሉ ሰጥቸዋለሁ።

ባሕራንም የቅዱስ ሚካኤልን መታሰቢያ ሲያደርግ ቀሲስ ሆኖ የቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ሲያገለግል ኖረ። ያን ጊዜ ማኑሄ የእግዚአብሔርን መልአክ መሆኑን አወቀ መሳ. ፲፫፡፳፩ እንዲል ባሕራን ከመንገድ ላይ የተገለጠለት የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ሚካኤልን መሆኑን አወቀ።

በመንገድህ ይጠብቅህ ዘንድ ወደ አዘጋጀሁልህ ስፍራ ያገባህ ዘንድ እነሆ መልአኬን በፊትህ እልካለሁ ስማው እምቢ አትበለው ስሜ በእርሱ ስለሆነ። ሁላችንንም ከክፉ ነገር ሁሉ ያድነን ወደ ተዘጋጀልን ሥፍራ እስክንገባ በክንፈ ረድኤቱ ይጠብቀን በአማላጅነቱና በተራዳኢነቱ እንማፀን።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፣ ወለወላዲቱ ድንግል፣ ወለመስቀሉ ክቡር። አሜን!

 ቀሲስ በለጠ ጓሉ

                        

 

 

 

 

ነገረ ማርያም ከሁለት ቃላት የተገኘ ነው። ነገር፣ የአንድን ትምህርት መግለጫ አጉልቶ የሚያሳይ ሲሆን ማርያም፣ የእመቤታችን መጠሪያ ስም ነው። በመሆኑም ነገረ ማርያም ማለት በእናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በኩል እግዚአብሔር ወዶ ፈቅዶ ለሰው ልጅ የገለጠውን ምሥጢር የምንማርበት ትምህርት ነው። ስለ እመቤታችን ያለው ትምህርት እጅጉን ሰፊ ስለሆነ በዚች መልእክት ላይ ነገረ ማርያምን ለማስፈር አይሞከርም። አባይን በጭልፋ ቀድቶ መጨረስ እንደማይቻል ሁሉ የእመቤታችንንም ነገር አስተምሮ ለመጨረስ አይቻልም። ነገር ግን በዚህ መልእክት ሦስት አበይት ነጥቦችን እናነሳለን። እነርሱም፦

፩. የቅድስት ድንግል ማርያም የትውልድ ሐረግ

፪. የድንግል ማርያም የስሟ ትርጓሜ

፫. እመቤታችን የምትታወቅባቸው ተጨማሪ ስሞች

 

፩. የቅድስት ድንግል ማርያም የትውልድ ሐረግ

እግዚአብሔር አምላክ ማደሪያው ሁሉ ንጹሕና ቅዱስ ፍጹምም ነው።ስለሆነም እርሱ ያደረበት ሰውም ሆነ ቦታ ወይም ንዋይ ሁሉ ቅዱስ ይባላል። እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የአምላክ ማደሪያ ሆና ስለተገኘች ቅድስት ትባላለች። የተገኘችውም እግዚአብሔር ካደረባቸው ቅዱሳን ስለሆነም ጭምር ቅድስት ተብላለች።

፪. የድንግል ማርያም የስሟ ትርጓሜ

ማርያም ማለት በዕብራይስጥ ቋንቋ ማሪሃም ከሚለው ቃል የተወሰደ ሲሆን ትርጉሙም የብዙኃን እናት ማለት ነው፤ አብርሃም

 

ማለት የብዙኃን አባት ማለት እንደሆነ። (ዘፍ. ፲፯፥፭) በቤተ ክርስቲያናችን ትምህርት የቤተ ክርስቲያናችን ሊቃውንት የቅድስት ድንግል ማርያምን ስም እንደሚከተለው ያመሰጥሩታል፦

ማርያም ማለት፦

ሀ. መርሕ ለመንግሥተ ሰማያት (ወደ መንግሥተ ሰማያት መርታ የምታገባ) ማለት ነው፦

የአዳም ዘር በሙሉ በኢየሱስ ክርስቶስ ቤዛነት ወደ ገነት የገባው ወይንም ወደ ቀደመ ክብሩ የተመለሰው ኢየሱስ ክርስቶስ የእርሷን ሥጋ ተዋሕዶ በመወለዱ ስለሆነ እንዲሁም ወደ ዘለዓለም ሕይወት የሚያስገባው ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙም ከርሷ የነሣው በመሆኑ ነው። በተጨማሪም የድንግል ማርያምን አማላጅነት ሳያምኑ መንግሥተ ሰማያት መግባት አይቻልምና ነው።

ለ. ጸጋና ሐብት ማለት ነው፦

የእመቤታችን ወላጆች ለጊዜው በመምከናቸው በሰው ዘንድ ተንቀው የነበሩ ሲሆን የእርሷ መወለድ ሀብት እና ጸጋ ሆኗቸዋል። ፍጻሜው ግን አማላጅነቷን ዐውቀው ቃል ኪዳኗን አምነው ለሚመጡ ምእመናን ሁሉ ሀብት እና ጸጋ ሆና ተሰጥታለች። (ዮሐ ፲፱፣ ፳፯) በበደሉ ምክንያት ከጸጋ እግዚአብሔር ተራቁቶ በእግረ አጋንንት ይቀጠቀጥ የነበረው አዳም ጸጋው ተመልሶለት ሀብተ መንፈስ ቅዱስን ገንዘብ ያደረገው በእመቤታችን በኩል ነው። “አዳም ከገነት በተባረረ ጊዜ ተስፋው አንቺ ነሽ” ብሎ አባ ሕርያቆስ በቅዳሴው ያመሰገናትም ለዚህ ነው። 

ሐ. በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ የጸናች ፍጽምት ማለት ነው፦

እግዚአብሔር በባሕርዩ ፍጹም አምላክ ስለሆነ ለምሥጢረ ሥጋዌ ሰው ይሆንባት ዘንድ በመለኮታዊ ጥበቡ የመረጣት በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ ፍጽምት ትሆን ዘንድ ይገባልና በሥጋም በነፍስም ፍጽምት አደረጋት።

መ. ከፍጡራን በላይ ከፈጣሪ በታች ማለት ነው፦

እግዚአብሔር በፈጠራቸው በመላእክትና በቅዱሳን ላይ በረድኤት ወይንም በጸጋ ነው ያደረባቸው። በድንግል ማርያም ላይ ግን በረድኤትና በጸጋ ብቻ ሳይሆን ከሥጋዋ ሥጋን፤ ከደሟ ደምን፤ ከነፍሷ ነፍስን ነሥቶ ነው የተገለጠው(ሰው የሆነው)። ለዚህም ነው መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል “አንቺ ከሴቶች መካከል የተባረክሽ ነሽ” ያላት (ሉቃ ፩፣፳፰)።  ስለሆነም ድንግል ማርያም ከመላእክትም ከቅዱሳንም ትበልጣለችና ከፈጣሪ በታች ከፍጡራን በላይ ተብላለች።

ሠ. የብዙዎች እናት ማለት ነው፦

አንድ ቤት የቤት እመቤትና አባወራ እንዳለው ሁሉ በክርስቶስ አምነው ላሉ ክርስቲያኖች ሁሉ እመቤታቸው (እናታቸው) ድንግል ማርያም ናት፤ የቤታቸው ራስ ልጇ አማኑኤል እንደሆነ ማለት ነው።

ረ. በእግዚአብሔርና በሰው መካከል የምትላላክ ማለት ነው፦

ለሰዎች በሥጋ ዘመዳችን ስትሆን ለፈጣሪ ደግሞ እናቱ ነች፤ በመካከል ሆና የምታገናኘን ወይንም የምታማልደን ስለሆነች በሰውና በፈጣሪ መካከል ያለች መካከለኛ ትባላለች። የሰውን ልመና ወደ እግዚአብሔር፣ የእግዚአብሔርንም ይቅርታ ወደ ሰው በማድረስ ድኅነተ ሥጋ ድኅነተ ነፍስ፣ በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስ እያማለደች ታሰጣለችና።

፫. እመቤታችን የምትታወቅባቸው ተጨማሪ ስሞች

እመ አምላክ      ወላዲተ አምላክ     

ኪዳነ ምሕረት    ቤዛዊተ ዓለም                          

እምነጽዮን          ሰአሊተ ምሕረት

ሶልያና               አዶናዊት

 

መጋቤ ሃይማኖት ቀሲስ አሐዱ አስረስ