ቅዱስ ቁርባን ከመቀበል አስቀድሞ ከቅዱስ ምሥጢር የሚቀበሉ ሁሉ እንዲህ ይበሉ፤

አቤቱ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! ርኵስት ከሆነች ከቤቴ ጠፈር በታች ትገባ ዘንድ የሚገባኝ አይደለም።

እኔ አሳዝኜሃለሁና  በፊትህም ክፉ ሥራ ሠርቻለሁና በአርኣያህና በአምሳልህ የፈጠርኸው ሥጋዬንና ነፍሴን ትእዛዝህን በማፍረስ አሳድፌአለሁና ሥራም ምንም ምን የለኝምና። ነገር ግን ስለ መፍጠርህና እኔን ለማዳን ሰው ስለ መሆንህ፣ ስለ ክቡር መስቀልህም፣ ማሕየዊት ስለ ምትሆን ስለ ሞትህ፣ በሦስተኛው ቀን ስለ መነሣትህም ጌታዬ ሆይ ከበደልና ከመርገም ሁሉ፣ ከኃጢአትና ከርኵሰትም ሁሉ ታነጻኝ ዘንድ እለምንሃለሁ እማልድሃለሁም።

የቅድስናህንም ምሥጢር በተቀበልኩ ጊዜ ለወቀሳ ለመፈራረጃ አይሁንብኝ ማረኝ ይቅርም በለኝ እንጂ።