በሦስተኛው ቀን በገሊላ ቃና ሠርግ ሆነ

ጥር 11 ቀን 2007 ዓ.ም

መ/ር ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ

kana zegelila 07 ወአርአየ ስብሐቲሁ ወአምኑ ቦቱ አርዳኢሁ  ጌትነቱን ገለጠ ደቀ መዛሙርቱም በእርሱ አመኑ” ዮሐ. 2፤11 በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የበዐላት አከባበር ቀመር ከበዓለ ልደት ፤ግዝረት፤ ጥምቀት ቀጥሎ ቃና ዘገሊላ ይከበራል፡፡ ምክንያቱም ክብር ምስጋና ይግባውና ጌታችን አምላካችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰውን ልጅ ለማዳን ወደዚህ ዓለም በመጣበት ወቅት ልዩ ልዩ የሆኑ ድንቅ ተአምራት አድርጓል፡፡ ከእነዚህም የመጀመሪያው በቃና ዘገሊላ በሰርግ ቤት ተገኝቶ ያደረገው ተአምር ተጠቃሽ ነው፡፡


ቅዱስ ዮሐንስ በወንጌሉ እንዲህ ጽፎታል፡፡ “በሦስተኛው ቀን በገሊላ ቃና ሠርግ ሆነ” ምን በሆነ በሦስተኛው ቀን የሚል ጥያቄ በሁላችንም እዕምሮ እንደሚመላለስ አያጠያይቅም፡፡ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በማየ ዮርዳኖስ በእደ ዮሐንስ ጥር 11 ቀን ተጠምቆ ሳይውል ሳያድር ዕለቱን ገዳመ ቆሮንቶስ ገብቶ አርባ መዓልትና አርባ ሌሊት ጾሞ ፤ዲያብሎስን ድል ነስቶ፤ መዋዕለ ጾሙን ፈጽሞ ለእኛም ዲያብሎስን ደል የምንነሳበትን መንገድ አሳይቶን ከገዳመ ቆሮንቶስ መልስ ደቀ መዛሙርቱን መረጠ፡፡ ከጥር አሥራ አንድ እስከ የካቲት ሃያ አርባ ቀን ይሆናል፡፡ መዋዕለ ጾሙን የካቲት ሃያ ፈጽሞ በወጣ በሦስተኛው ቀን ገሊላ አውራጃ ቃና በተባለች መንደር ሰርግ ሆነ፡፡ በዚህ ሰርግ ብዙ ሰዎች የታደሙ መሆኑን የወይን ጠጁ ማለቅ ያስረዳል፡፡ በእርግጥም የተጠሩት ሰዎች ብዙ ቢሆንም ብዙዎች መመገብ የሚችል አምላክ በሰርግ ቤት መጠራቱ ልዩ ያደርገዋል፡፡ በዚህ ሰርግ ከሠዎች በተጨማሪ ሦስት አካላት ተጠርተዋል፡፡

 

1. እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም

“ወሀለወት ህየ እሙ ለእግዚእ ኢየሱስ ክርስቶስ” የጌታ እናት ከዚያ ነበረች እንዲል እንዲያው ዝም ብሎ አይደለም፡፡ በደግ ሰው ልማድ ተጠርታ እንጂ እመቤታችን በማኅበራዊ ሕይወት የነበራትን ተሳትፎ እና በሰዎች ዘነድ የነበራትን ተዋቂነት ያመለክታል፡፡ በሌላ መልኩ በቤተ ዘመድ ልማድ ማንኛውም ዘመድ እንደተጠራው ሁሉ እርሷም በገሊላ በነበሩት ሰዎች ዘንድ ታላቅና ተዋቂ ስለበረች እና ቤተ ዘመድ በመሆኗ በዚህ ሠርግ ተጠርታ ነበር፡፡የተገኘችው የሰው ሰውኛው ይህ ቢሆንም በዚያ ሠርግ ቤት ማንም ሊሠራው የማይችል የሥራ ድርሻ ነበራት፡፡ይህ በሰዎች ዘንድ የማይታወቅ በእግዚአብሔርና በእርሷ መካከል ያለ አማላጅነት ነው፡፡

 

የጎደለውን መሙላት ለሚችል ውድ ልጇ የጎደለውን እንዲሞላ ማማለድ ነው ፡፡ እመቤታችን ከሰው ልጆች የተለየች ክብርት ቅድስት ንፅህት ልዩ በመሆኗ የምታውቀውም ምሥጢር ከሰው የተለየ ነው፡፡ “ወእሙሰ ተአቀብ ዘንተ ኩሎ ነገር ወትወድዮ ውስተ ልበ” ማርያም ግን ይህንን ሁሉ ትጠብቀው በልቧም ታኖረው ነበር ሉቃ.2፡19 ይህን ሁሉ ያለው ድንግል ማርያም አምላክን በመውለዷ ከሰው ልጆች የራቀ ምስጢር የተገለጠላት መሆኑን ያስረዳል፡፡ ይህንን ሁሉ ብሎ እንደ ሸማ ጠቅልሎ እንደ ወርቅ አንከብሎ የተናገረው የተገለጠላት ምስጢር በሰው አንደበት ተነግሮ የማያልቅ እንደሆነ ነው የሚገልጠው፡፡ ምክንያቱም አንድ ሁለት ብለን የምንቆጥረው አይደለምና መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል እንደዚሁ “ፀጋን የተሞላሽ” በማለት የገለጠው ለእርሷ የተሰጠው ባለሟልነት ልዩ መሆኑን ለማስረገጥ ነበር፡፡ ከዚህ የተነሳ በሠርጉ ቤት የምትሰራውን ሥራ በውል ታውቅ ነበርና፡፡

 

2. ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተጠርቶ ነበር

“ወፀውእዎ ለእግዚእ ኢየሱስ ክርስቶስ” ጌታ ኢየሱስንም ጠሩት” ዮሐ.2፤2 እናትን ጠርቶ ልጅን መተው ተገቢ አይደለምና እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ጠርተው ልጇም ጠርተውታል፡፡ ይህም ፍፁም ሰው መሆኑን ያስረዳል፡፡ ሰው ነውና እንደ ሰውነቱ ወደ ሰርግ ቤት ተጠራ፤አምላክ ነውና ጌትነቱን ገለጠ፡፡

 

ከሚደሰቱት ጋር መደሰት ከሚያዝኑ ጋር ማዘን ተገቢ መሆን በቃል ብቻ ሳይሆን በተግባር አስተማረ፡፡ በቃና ዘገሊላ ከሠርግ ቤት እንደሄደ በአልአዛር ቤት ለለቅሶ መገኘቱን ልብ ይሏል፡፡ወደ ሠርግ ቤት የሄደው በደስታ ነበር፡፡ ቅዱስ ያሬድ እንደገለጠው “ሖረ ኢየሱስ በትፍስህት ውስተ ከብካብ እንዘ ይገብር ተአምረ ወመንክረ በውስተ አህዛብ፤ ኢየሱስ በአህዛብ ፊት ተአምራትንና ድንቆችን እያደረገ በደስታ ወደ ሠርግ ሄደ” ወደ አልአዛር ቤት ሲሄድ ግን “ጌታች ኢየሱስ ክርስቶስም እርሷ (ማርታ) ስታለቅስ ባየ ጊዜ በልቡ አዘነ፡፡በራሱም ታወከ(ራሱን ነቀነቀ፡-የሀዘን ነው) ጌታችን ኢየሱስም እንባውን አፈሰሰ ፡፡አይሁድም ምን ያህል ይወደው እንደነበር እዩ አሉ” ዮሐ.11÷33-38

 

ከዚህ እንደ ምንመለከተው ከኀጢአት በቀር የሰውነትን ሥራ መሥራቱን የሰውን የተፈጥሮ ሕግ ምን ያህል እንደ ከበረ እና እንደፈጸመ ያሳያል በመደሰት እና በማዘን ፍጹም ሰው መሆኑን ሲያስረዳን ፍጹም አምላክ መሆኑን በሰርጉ ቤት ውኃውን የወይን ጠጅ በማድረግ በልቅሶ ቤትም ዓልዓዛርን ከአራት ቀናት በኋላ በማስነሣት አስረዳን፡፡ አምላክ ነኝ ከሠርግ ቤት አልሄድም ከልቅሶም ቤት አልገኝም አላለም በትሕትና ራሱን ዝቅ አድርጎ በሰርግ ቤት እንዲሁም የሚያዝኑትን ለማጽናት በልቅሶ ቤት በመገኘቱ ሁሉንም የሰውነት ሥራ አከናወነ፡፡ አምላክ ነው በሰርግ ቤት የጎደለውን መላ፡፡ አምላክ ነውና የሞተውን አልዓዛርን መግነዝ ፍቱልኝ መቃብር ክፈቱኝ ሳይል እንዲነሣ አደረገ፡፡

 

በዚህ የሰርግ ቤት ባይገኝሰዎች ምን ያህል ሀፍረት ይሰማቸው ይሆን? የእርሱ እንዲሁም የእናቱ በሰርጉ ቤት መገኘት ለባለሰርጉና ለታዳሚዎች ሙላት ነበር እርሱ ባይኖር የሰርጉ ቤት የሃዘን ቤት ሊሆን እንደሚችል ምንም ጥርጥር የለውም በዚህ ሰርግ ቤት ተመላጅነት የአምላክ አማላጅነት ደግሞ የፍጡራን መሆኑን አስተምሯል፡፡

 

“ወሶበ ሀልቀ ወይኖ ወይትቤሎ እሙ ወይንኬ አልቦሙ” ዮሐ.3÷3 “የወይን ጠጅ ባለቀባቸው ጊዜ እመቤታችን የወይን ጠጅ እኮ የላቸውም” አለችው አማላጅነት የፍጡራን ገንዘብ ነው፡፡ እርሱ አንቺ ሴት ከአንቺ ጋር ምን አለኝ÷ ጊዜዬ ገና አልደረሰም አላት” ከአንቺ ጋር ምን ጠብ አለኝ አንቺ ያልሽውን ልፈጽም አይደለም ሰው የሆንኩት አላት ጊዜ ገና አልደረሰም የሚለው ሥራውን ያለ ጊዜው አይሠራውምና ነው፡፡ ለእግዚአብሔር የሥራ ጊዜ አለው” እንዲል፡፡ መዝ.118÷126 በሌላ መልኩ በአምላክነቱ ማንም የማያዝዘው ግድ ይህን አድርግ ብሎ ማንም ሊያሰገድደው የሚችል የወደደውን የሚያደርግ ቢፈልግ የሚያዘገይ ሲፈልግ በዐይን ጥቅሻ በፈጠነ መልኩ መፈጸም የሚችል በራሱ ፈቃድ እንጂ በሰምች ፈቃድ የማይመራ መሆኑን ያስተምረናል፡፡

“ፈቃድ በሰማይ እንደሆነች እንዲሁ በምድር ትሁን” ማቴ.6÷ ብላችሁ ለምኑኝ ያለው ለዚህ ነው በሌላ መንገድ የወይን ጠጅ በሙሉ አላላቀም፡፡ ያለውን ቢያበረክተው ተአምራቱን አናደቅም፥ ፈጽሞ ጭል ብሎ እስከሚያልቅ “ጊዜ ገና አልደረሰም” አለ፡፡ሰው ቢለምን ቢማልድ በእርሱ ፈቃድ ጊዜው ሲደርስ ነው የሚፈጸመው፡፡ምልጃው አልተስማም ተቀባይነት አላገኝም ማለት ግን አይደለም ተቀባይነት ያገኘ መሆኑ የሚታወቀው በመደረጉ ነው፡፡

 

አማላጅ ያስፈለገው እርሱ የሚያውቀው ነገር ኖሮት በስምአ በለው ለመንገር አይደለም ለሰው ልጆች ያለው ፍቅር ይታወቅ ዘንድ እና የሰው ልጆችን ከችግር የሚያወጣበት መንገዱ ብዙ መሆኑን ለማስረዳት ነው እንጂ፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሚዜዎችን “ኩሎ ዘይቤለክሙ ግበሩ፤ያዘዛችሁን ሁሉ አድርጉ፡፡” ማለቷ “አንቺ ሴት ከአንቺ ጋር ምን አለኝ” የሚለው የጌታችን መልስ “እሺታ ይሁንታን” የሚገልጽ መሆኑን ያስረዳል፡፡ “እሱም ውኃ ቅዱና ጋኖችን ምሏቸው” አለ፡፡ እነርሱም በታዘዙት መሠረት እመቤታችን ያላችሁን አድርጉ እንዳለቻቸው ውኃውን ቀድተው ጋኖችን ሞሏቸው፡፡ ውኃውንም ክብር ይግባውና በአምላካዊ ችሎታው ወደ ወይን ጠጅ ለወጠው፡፡ ለአሳዳሪውም ሰጠው አሳዳሪው የወይን ጠጅ የሆነውን ውኃ ቀምሶ አደነቀ ከወዴት እንደመጣ ግን አላወቀም ድንቅ በሆነ አምላክ ሥራ እንደተለወጠም አልተረዳም፡፡ ያን ምስጢር የሚያቀው ባለሰርጉ፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፣ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምና ውኃውን የቀዱ ሰዎች ናቸውና፡፡

 

ታዳሚዎችም “ሰው ሁሉ የተሻለውን ወይን አስቀድሞ ያቀርባል በኋላም ተራውን የወይን ጠጅ በኋላ ያቀርባል አንተስ መናኛውን ከፊት አስቀድመህ ያማረውን ከኋላ ታመጣለህን” ብለው አድንቀዋል፡፡ ድሮም የአምላክ ሥራ እንደዚያ ነው ብርሃን ከመፍጠሩ አስቀድሞ ጨለማን ፈጥሯል ከጨለማ ቀጥሎ “ብርሃን ይሁን” በማለት ብርሃንን ፈጥሯል፡፡ መጀመሪያ ብርሃን ተፈጥሮ ኋላ ጨለማ ቢፈጠር ይከብድ ነበርና መጀመሪያ 21 ፍጥረታት ፈጥሯል፡፡ በመጨረሻም በአርዓያውና በአምሳሉ የሥነ ፍጥረት የሆነውን የሰው ልጅ ፈጥሯል፡፡ ናትናኤልንም እንዲህ ብሎታል፡፡

 

“ከእንግዲህ ወዲህ ከዚህ የሚባልጥ ታያለህ” ማለቱ የእግዚብሔር ሥራ እየቆየ ውብ ያማረ መሆኑን ያመለክታል ሰው ግን ጥሩ ነው፡፡ ያለውን ያስቀድማል ያ ሲያልቅ የናቀውን ይፈልጋል፡፡ “የወደዱትን ቢያጡ ያጡትን ይቀላውጡ” እንዲሉ እግዚብሔር ልማዱ ነው፡፡ ተራውን ከፊት ታላቁን ከኋላ ማድረግ ለሰው መጀመሪያ የተሰጠው የሚያልፈው ዓለም ነው በኋላ የማያልፈው መንግሥተ ሰማያት ይሰጠዋል ሰው መጀመሪያ ይሞታል በመጨረሻ ትንሣኤ አለው፡፡ ሰው መጀመሪያ ሲወለድ ርቀቱን ነው፡፡ ኋላ ልብስ ያገኛል፡፡ ሁብታም ይሆናል፡፡ ሰው ወደዚህ ዓለም ሲመጣ ዓለምን የሚያገኛት የሚተዋወቃት በልቅሶ ነው፤ ኋላ ግን ይደሰታል በሀሳር በልቅሶ ወደመቃብር ይወርዳል፡፡ በደስታ “መቃብር ክፈቱልኛ፥ መግነዝ ፍቱልኝ” ሳይል ይነሣል ይህን የአምላክ ሥራ አድንቆ መቀበል እንጂ መቃወም አይችልም፡፡

 

3. ቅዱሳን ሐዋርያት በዚህ ሠርግ ነበሩ

“ወለአርዳኢሁ ውስተ ከብካብ” እንዲል፡፡ ዮሐ.2፥2 “ደቀመዛሙርቱንም ጠሯቸው” መምህርን ጠርቶ ደቀ መዝሙርን መተው ተገቢ አይደለምና፤ ደቀ መዛሙርቱ ከመምህራቸው ከክርስቶስ ጋር አብረው በሠርግ ቤት ተገኝተው በተደረገው ተአምር ጌትነቱን አምነዋል፡፡ ተአምራቱን ተመልክተዋል፣ ከዋለበት የሚውሉ፥ ከአደረበት የሚያድሩ፥ ተአምራት የማይከፈልባቸው፥ ይህን ዓለም ለማስተማር የተመረጡ ናቸውና፤ አየን ብለው እንጂ ሰማን ብለው አያስተምሩምና፡፡በጠቅላላው የእነርሱ በሰርጉ ቤት መገኘት የሚያስተምርና ካህናት የሌሉበት ሰርግ ሊደረግ እንደማይገባው ነው፡፡ በሰርግ ቤት የካህናት መገኘት እና ቡራኬ መስጠት አስፈላጊ መሆኑን ያስተምራል፡፡

 

በፍትሐ ነገሥት አን.24 የተገለጸውም ይህ ነው “ወማዕሰረ ተዋሰቦሶ ኢይትፌጸም ወኢይከውን ዘእንበለ በሀልዎተ ካህናት ወጸሎት ዘለዕሌሆሙ” የጋብቻ አንድነት ካህናት ቢኖሩ እንጂ ያለእነርሱ አይጸናም ጸሎት ቢያደርጉ እንጂ ያለ ጸሎት አይፈጸምም” እን. በቃና ዘገሊላው ሰርግ ጋብቻን በጥንተ ፍጥረት “ሰው ብቻውን ይሆን ዘንድ መልካም አይደለም ረዳት እንፍጠርለት” ዘፍ.2፥19 ያለ አምላክ የሐዲስ ኪዳን ጋብቻ በካህናት ቡራኬና ጸሎት መከናወን እንደሚገባው ሲያስተምረን ቅዱሳን ሐዋርያትን ይዞ ተገኝቷል፡፡ የቃና ዘገሊላ ሰርግ እና በሰርጉ ላይ የታዩ ተአምራት ምልጃዎች ሁሉ ሌላም ምሥጢር ያዘሉ ናቸው፡፡ እመቤታችን “የወይን ጠጅ እኮ የላቸውም” ማለቷ “ወይን” በተባለው የክርስቶስ ደም ዓለም እንዲድን ያስረዳል፡፡ ደምህን አፍሰህ ሥጋህን ቆርሰህ አጽናቸው ማለቷ ሲሆን “ጊዜዪ ገና ነው” የሚለው የጌታ መልስ “ደሙ በዕለተ ዓርብ የሚፈስበት ጊዜ ገና መሆኑን ያስረዳል” ጥንቱን ዓለምን ለማዳን አይደለምን፣ ሰው የሆንኩት ሥጋ የለበስኩት ለዚህ ዓለምን ለማዳን አይደለምን ሲል ነው፡፡

 

Read more http://www.eotcmk.org/site/-mainmenu-24/--mainmenu-26/1697-2015-01-17-07-07-33