ለተገደለው Mr. GEORGE FLOYD የተሰማን ጥልቅ ኀዘን

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

ክርስቶስ ተንሥዓ እሙታን!
ግንቦት ፳፫/፳፻፲፪ ዓ/ም

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ርእሰ አድባራት ጽርሐ-አርያም ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል እና በውስጥዋ የምንኖር መላው ካህናት እና ምዕመናን በዘግናኝና አሰቃቂ እንዲሁም ፍጹም ኢሰብዓዊ በሆነ ሁኔታ ሰኞ ግንቦት ፲፯/፳፻፲፪ ዓ/ም (May 25, 2020) በግፍ ለተገደለው Mr. George Floyd የተሰማንን ጥልቅ ኀዘን በውስጣችን ይዘን ሳንናገረው በዝምታ የምናልፈው ስላይደለ ከዚህ እንደሚከተለው እንገልጻለን።

እጁን የፊጥኝ ታስሮ፣ ዕግሩ እንዳይላወስ በግድ ተይዞ፣ የደም ቱቦ መተላለፊያው አንገቱ ላይ ለስምንት ደቂቃ ከአርባ ስድስት ሰከንድ ያህል ከመሬቱ ጋር በጨካኝ ሰው ጉልበት ተሰፍቶ ምንም መላወስ በማይችልበት ሁኔታ ውስጥ በሚያሳዝን ሲቃ «እባክህ መተንፈስ አልቻልኩም፤ ሆዴ፣ አንገቴና ሁለመናዬ ተጎድቷል፤ ሊገድሉኝ ነው» እያለ ሲጮህ መልስ አልባ የነበረው የ፵፮ ዓመት ሰው ከዚያ ሁሉ ሥቃይ በኋላ ከሞት የሚያስጥለው ወገን አጥቶ መከራውንና ሥቃዩን ለብቻው ታግሎ ትንፋሽ አልባ ሆኖ ላይመለስ አሸልቧል። ከልመና በስተቀር አንዳች ማድረግ እንደማይቻል ተረድቶ በተደጋጋሚ ቢማጸንም ያቺ ቀን ነፍሱ ከሥጋው የምትለይባት በመሆኗ የሞት ጽዋ ከመቅመስ የልመና ቃሉም ሆነ አሳዛኝ ሲቃው ሳይራዱት ቀሩ።

ይኽ ዜና ተደብቆ የማይቀር ሆነና በተለያዩ ማኅበራዊ ድረ ገጽ ላይ ወጥቶ ለሕዝብ ዕይታ ሲደርስ በቀን በአደባባይ እንዲህ ያለው ድርጊት መፈጸሙ በጠቅላላው የዓለምን ሕዝብ በተለይም መላው አሜሪካንን ክፉኛ አስቆጣ። በእያንዳንዱ ቤት ውስጥ እንዲሁም በእያንዳንዱ ዓይንና ጆሮ የዚህ ጭከና የተሞላበት ግድያ መድረሱ፣ መታየቱና መሰማቱ በወላጆችና በልጆች መካከል ጥያቄ አጫረ። ክቡር የሆነና በእግዚአብሔር እጅ ተፈጥሮ የእግዚአብሔር እስትንፋስ በውስጡ ያለበት «ሰው» የሚባል ፍጥረት በሕይወት መኖሩ ለክፉዎች እንደ ምንም ተቆጥሮ ነፍሱ ስትነጠቅ ማየት በሁሉ ዘንድ ታላቅ ስጋትን ፈጠረ።

በወላጆች በኩል «የነገ ተረኛ እኛና ልጆቻችን ነን» ሲባል በልጆች በኩል ደግሞ «የነገ ተረኛ እኛና ወላጆቻችን ናቸው» ማለት በእያንዳንዱ ቤተሰብ ውስጥ ያለ ቋንቋ ሆኖ ተሰማ። Mr. George Floyd ከስድስት ቀናት በፊት ዳግም ላይመለስ ቢያሸልብም በእንዲህ ያለ አሟሟት ምድሪቱን መሰናበቱ ግን በብዙዎች ዘንድ ሲታወስ እንዲኖር ያደርጉታል።

ይኽ ከፍተኛ ቁጣ የቀሰቀሰው ዜና ከተሰማበት ቀን ጀምሮ በማንኛውም የዓለም ዜና መሰራጫ እየተላለፈ ከትንሽ እስከ ትልቅ ድረስ ሁሉም አይቶት፤ ከአዳጊ ወጣቶች ጀምሮ እስከ አረጋውያን ድረስ ሁሉም በድርጊቱ አዝኖ ደረቱን በቁጭት ሲደቃና ተስፋ በመቁረጥ ስሜት ውስጥ ገብቶ በኃይል መነሣቱን ተመልክተናል።

ዛሬ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን፦
* ይኽንን እኲይ ግብር ፍጹም ኀዘን በተሞላው ሁኔታ ትገልጸዋለች።
* የምታስተምረው ወንጌል እንዲህ ያለውን ድርጊት ያወግዛልና በፍጹም ትኮንነዋለች።
* ኃይልዋም ጉልበትዋም እግዚአብሔር ነውና ሁሉን ማድረግ ወደሚችለው አቤት ትላለች።
* ልጆቿን ሰብስባ ታጽናናለች፤ ትመክራለች፤ ታስተምራለች።
* ለተገፋውና ለወደቀው ድምጽ ናትና በሞት ለተለየው ጸሎትዋን ወደ አምላክዋ ታቀርባለች።
* ፍጹም መጽናናት የሚገኘው ከእግዚአብሔር ነውና ፍትህ በምድር ላይ ነግሦ እንዲኖር ያለማቋረጥ ወንጌለ ክርስቶስን ትሰብካለች።
* የምታስተምራቸው ልጆቿ ወደፊት የሰላም አምባሳደር ሆነው በዓለም ስማቸው እንዲጠራና በመልካም ሥነ-ምግባር ታንጸው ምሳሌ እንዲሆኑላት ትፈልጋለች።
* ልጆቿ የችግር ሳይሆን የመፍትሔ አካል ሆነው ዘረኝነትን በመዋጋት «ሰው ተብሎ የተጠራ ሁሉም የእግዚአብሔር ፍጥረት ያለ አድልዎ በእኩልነት እንዲኖር ከሚያስቡና ከሚሠሩ ሰዎች መካከል እንደ አንዱ ሆነው እንዲታዩላት ታበረታታለች።
* ወጣቶች ኀዘናቸው ሲያበቃ ወደፊት ምን ማድረግ አለብን በማለት በታላቅ ራእይ ተነሥተው ከበጎ ነገር ጋር የሚተባበሩና ራስን በመግዛት አትራፊ እንዲሆኑ ጥሪዋን ታቀርባለች።

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ከላይ ከብዙ በጥቂቱ የተዘረዘሩትን ነጥቦች ለልጆችዋ ስትገልጽ ልጆችዋ በዚህ ፋና ብርሃን ዕንቅፋቱን እያለፉ መውደቃቸውን ሳይሆን መነሣታቸውን፣ ማዘናቸውን ሳይሆን ደስታቸውን፣ ጅማሬአቸውን ሳይሆን ፍጻሜያቸውን አስበው እንዲጓዙላት በማሰብ ነው።

በመጨረሻም ቤተ ክርስቲያን ይኽንን እኲይ ተግባር የምታወግዘው የሕይወት መመሪያ ይሆንልን ዘንድ በተሰጠን መጽሐፍ ቅዱስ ላይ እግዚአብሔር ከሚጠላቸው ድርጊቶች አንዱ ንጹሕ ደም ማፍሰስ በመሆኑ ነው። አምስቱ ውሾች ተብለው ከተጠቀሱት መካከል አንዱ ነፍሰ ገዳይነት ስለሆነ ነው። ከአሥራ ስድስቱ የሥጋ ሥራዎች አንዱ መግደል ሆኖ ስለተጠቀሰ ነው። ከአሥርቱ ትዕዛዛት አንዱ አትግደል ስለሚልም ነው።

አሁንም ይኽንን እኩይ ምግባር እየተዋጋን ከመለያየት ይልቅ ወደ አንድነት የምንመጣበት መንገድ ላይ እየሠራን መኖርን መለማመድ ያስፈልገናል። መለያየቱ የሚጎዳን ሁላችንንም ስለሆነ በተቻለ መጠን ከላይ እንደገልጽነው የመፍትሔው አካል በመሆን ከችግሩ የምንማርበት እንጂ ተስፋ የምንቆርጥበት እንዳይሆን እናሳስባለን። ወላጆች ወደ አሜሪካን ምድር በተለያዩ ዓይነት ሁኔታዎች ከተለያዩ ቦታዎች መጥተን ነዋሪ ብንሆንም ልጆቻችን ደግሞ በዚህ ምድር ተወልደው የትውልድ አገራቸው ሆኗልና አስተማማኝ ፍትህ ነግሦ ሰው በጥፋቱ እንጂ በቀለሙ ምክንያት የማይቀጣበት፣ የማይጉላላበትና የማይገደልበት ምድር እንዲኖረን ሁላችን በጋራ ልንመክርበት ያስፈልገናል።

በተለይ ልጆቻችንን በሚማማሩበት እና በሚሠሩበት ቦታ ያለ ምንም መሳቀቅ መኖር የሚችሉት ችግሩን ብቻ ሳይሆን መፍትሔውን ፈላጊዎች ሆነው መትጋት ሲችሉ ብቻ ነውና በመምከርና በማስተማር ወላጆች የድርሻችንን እንወጣ፤ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም ዘወትር በጸሎትዋ እያገዘች ለዘላለም ትኑር።

ለሟች ቤተሰብ ልዑል እግዚአብሔር መጽናናት እንዲሰጥልን ያለውም የሰላም መደፍረስ ተወግዶ ሰላማዊ የሆነ ኑሮ እንድንጀምር አምላካችን ይርዳን።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!!