የፕሮቴስታንት እይታ ወጌሻ የሌለው የምላስ ወለምታ

ውድ አንባቢዎቻችን ከላይ ያስነበብኳችሁ ርዕስ በጥንቃቄ ካያችሁት ቀጥሎ ያለው ንባብ በትክክል ይገለጥላችኋል፡፡ ይህን ርዕስ የሰጠሁበትም ምክንያት ፕሮቴስታንት ወገኖቻችንን ለመንቀፍ ሳይሆን አመለካከታቸውን ወደ ትክክለኛው መስመር እንዲመልሱ ለማለት አስተያየት ለመስጠት ያህል ነው፡፡ መልካም ንባብ፤

የክርስቲያን ህብረት የሚባሉትን ሃይማኖተኞች ባጠቃላይ ወይም ክርስቶስን የሚያመልኩ ሃይማኖተኞችን ሁሉ አንድ የሚያደርጋቸው በጋራ የሚጠቀሙት መጽሐፍ ቅዱስ ነው፡፡ ይሁን እንጂ ከግማሽ በላይ የሚሆኑ ሃይማኖተኞች መጽሐፍ ቅዱስን የሚተረጉሙት በተመቻቸውና አንዳንዴም በአኗኗራቸው በሚስማማ መልኩ ነው ይህ ደግሞ ስህተት ከመሆኑም በላይ ሰዎች ወንጌልን ወንጀል እንዲያደርጉ መንገድ ይከፍታል፡፡

ለዛሬ የዮሐንስ ወንጌል ምዕ 2፡1-6 ያለውን ንባብ እንመልከት በሦስተኛውም ቀን በገሊላ ቃና ሰርግ ነበረ የኢየሱስም እናት በዚያ ነበረች ኢየሱስም ደግሞ ደቀ መዛሙርቱም ወደ ሰርጉ ታደሙ፡፡ የወይን ጠጅም ባለቀ ጊዜ የኢየሱስ እናት የወይን ጠጅ እኮ የላቸውም አለችው፡፡ ኢየሱስም አንቺ ሴት ከአንቺ ጋር ምን አለኝ ጊዜዬ ገና አልደረሰም አላት እናቱም ለአገልጋዮቹ የሚላችሁን ሁሉ አድርጉ አለቻቸው ዮሐ ፡-፤

እንግዲህ ይህንን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ካነበብን በኋላ እንደየአቅማችን እንረዳለን፡፡ ይሁን እንጂ እንደ ኦርቶዶክሳዊያን አፈታት ካየን በኋላ ወደ ፕሮቴስታንት አፈታት አንሄዳለን፡፡

ኦርቶዶክስ

የጌታ እናት ማርያም በታሪኩ ውስጥ እንደምንረዳው ወደ ሰርጉ ከታደሙት እንግዶች መካከል አንዷ ናት፡፡ በዚያ ስፍራ በርካታ የተከበሩ ባለሥልጣናት እና የቤተ መቅደስ አገልጋዮች እንዲሁም ባለፀጎች እና በልዩ ልዩ ሙያ የተካኑ ሰዎች እንደሚኖሩ መገመት አያዳግትም፡፡

ይሁን እንጂ ከነዚያ ሁሉ እድምተኞች መካከል የሰርግ ቤቱን ባለቤት ጭንቀት የተረዳችው ታውቅም፡፡ የነበረችው ድንግል ማርያም ብቻ ነበረች፡፡

በዚህም የጭንቅ ጊዜ አማላጅ መሆኗን እናውቃለን፡፡ እናምናለንም፡፡ የቤቱ ሰዎች እንኳ መጥተው የወይን ጠጅ አልቆብናልና እባክሽን ልጅሽን ለምኚልን አላሉም ነበር፡፡ ነገር ግን የአምላክ እናት ስለሆነች ይህን ቀላል ነገር ማወቅ ከርሷ ክብር ጋር ሲነጻጸር እጅግ በጣም ቀላሉ ነገር ነው፡፡

በዚያ ሥፍራ ከነበሩት እና ለጌታ ቅርብ የነበረች እናቱ ቅ/ድ/ማርያም መሆኗን ማመን ያስፈልጋል ይህ ማለት እመቤታችን ቅ/ድ/ማርያም የተመረጠችው በእግዚአብሔር ምርጫ በመሆኑ የወይን ጠጅ አልቋልና ያለቀውን መልስህ ሙላ በማለት እግዚአብሔር ለሆነው ልጇ ለኢየሱስ መናገር ለሌሎቹ ሊከብድ ይችላል እንጂ ለወለደችው ጡትም ላጠባችው በጀርባዋም ላዘለችው ለድ/ማርያም የማይከብድ ነው፡፡

1. ጌታም ሲመልስላት አንቺ ሴት ካንቺ ጋር ምን አለኝ በማለት የመለሰው የእስራኤል የአነጋገር ዘይቤ ሲሆን አንድን የተጠየቁትን ጥያቄ ለማጽናት እና ተቀባይነቱን ለማስረገጥ ሲፈልጉ የሚጠቀሙበት ቋንቋ ነው፡፡

ይህ ማለት አንቺ ሴት ከአንቺ ጋር ምን አለኝ ሲል

ሴት የሚለው ትርጉም ሥጋሽ ከሥጋዬ አጥንትሽ ከአጥንቴ የሚል ትርጉም ስላለው ከሥጋሽ ሥጋ ነስቼ ከነፍስሽም ነፍስ ነስቼ የተወለድኩ አይደለሁምን ምን ልታዘዝሽ የሚል የትህትና ቃላትን ያዘለ ንግግር ነው፡፡

በሌላ መልኩ ስናየው ደግሞ ከሥጋዋ ሥጋን ከነፍሷ ነፍስን ነሳ ማለት እናቴ ሆይ እያላት ነው ማለት ነው፡፡ ስለዚህ አናቴ ሆይ ስለምን ትለምኚኛለሽ እንደቀድሞው ልጅሽ ነኝና እዘዢኝ ማለት ነው፡፡

በዚህ መልኩ ከተግባቡ በኋላ የሚላችሁን አድርጉ በማለት መለሰችላቸው በዚህ አባባሏ ውስጥ የምረዳው ሌላው ጉዳይ አንደሚያዛቸውና እነርሱም የሚታዘዙትን ማድረግ እንዳለባቸው ጉዳዩ ከመጀመሩ በፊት ድንግል ማረያም ታውቅ ነበር ማለት ነው ስለዚህ ልመና ብቻ ሳይሆን ያቀረበችው ትእዛዝም ጭምር ነው፡፡ ልጇን ማዘዝ መብቷ ነውና፡፡

ሌላው ልንረዳው የሚያስፈልገን ጉዳይ ሴት የሚለው ቃል ከጌታ በቀጥታ በመጠሪያነት የተሰጠው ለወለደችው ለድንግል ማርያም ስለሆነ ቀጥታ ትርጉሙ እናት የሚል ይሆናል ማለት ነው፡፡ ምክንያቱም አንቺ ሴት ሲል እናቱን በመጥራት ላይ ነበረና፡፡

አመክንዮ (Logic)

በተነበበው ታሪክ ውስጥ የማርያም ምልጃ ወይም ትእዛዝ ተቀባይነት ባያገኝ ኖሮ ጌታ ኢየሱስ ውኃውን ወደ ወይን ጠጅ ባልለወጠው ነበር፡፡ ስለዚህ የማርያም ምልጃ ሙሉ በሙሉ በልጇ ዘንድ የተወደደና ተቀባይነት ነበረው፡፡
ማሳሰቢያ፡-

- ማርያም ስለ ቅድስናዋ ቅድስት
- ስለድንግልናዋ ድንግል በመሆኗ ምክንያት ለጽሑፍ ለመጠቀም ካልሆነ በስተቀር በኦርቶዶክሳዊ አጠራራችን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ብለን እንጠራለን፡፡ ይህ ማለት ግን ማርያም የሚለው ስም ብቻውን በቂ አይደለም በማለት ስም ለማወፈር ሳይሆን ለዘላለም ቅድስት እና ድንግል መሆኗን ለመግለጽ ነው፡፡ ሌሎች ሴቶች ከወለዱ በኋላ ድንግል ሊባሉ ስለማይችሉ የእርሷ ግን ከአእምሮ በላይ ዕፁብ ድንቅ ስለሆነ፡፡

በፕሮቴስታንት እይታ

1. ከላይ ያነበብነው ታሪክ በፕሮቴስታንት እይታ የማርያም ክብር የተነካበትና የምልጃን ሥራ ለመሥራት ሞክራ ሳይሳካላት መቅረቱን የሚያመላክት ነው፡፡

2. ኢየሱስ ማርያም የነገረችውን ሃሳብ አለመቀበል ብቻ ሳይሆን ከዚያም አልፎ አንቺ ሴት እያለ አንቋሽሿታል የሚል ነው፡፡

እንግዲህ እንዲህ ከሆነ በጥንቃቄ ሊታዩ የሚገባቸው ጉዳዮች አሉ፡፡

1ኛ. የቅ/ድ/ማርያም የቅድስና ደረጃ፤

የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የቅድስና ደረጃ ተራ ሰው ከሚደርስበት የቅድስና ደረጃ በላይ ነው፡፡ ይህ ማለት አንድ ሰው እግዚአብሔርን በማምለክ ቢጸና በቅድስና ሕይወት ቢመላለስ ጻድቅ ቅዱስ እየተባለ ሊጠራና በጸሎቱ ኃይል ሊያደርግ ወይም ሊያማልድ ከእግዚአብሔር ፀጋን ይቀበላል፡፡

ይህ በመሆኑ የእመቤታችን ቅ/ድ/ማርያም የቅድስና አገልግሎት በታችኛው ደረጃ ላይ ከሚገኘው የቅድስና ተግባር አልፋ የአምላክ እናት ሆኖ የማገልገል የቅድስና ደረጃ ላይ ደርሳለች፡፡ በዚህም የተነሳ ከፍጡራን ሁሉ በላይ ከፈጣሪ በታች ትባላለች ስለዚህ ድ/ማርያም ታማልዳለች ወይስ አታማልድም ብሎ መጠየቅ የዕውቀት ማነስ ካልሆነ በቀር ሌላ ሊሆን አይችልም፡፡

ምክንያቱም እርሷ ከማማለድ አልፋ የአምላክ እናት ሆናለችና፡፡

2ኛ. በዚህ የፕሮቴስታንት እይታ ውስጥ እየተሰደበ ወይም እየተዋረደ ያለው አካል ድንግል ማርያም ሳትሆን ጌታ ኢየሱስ ነው፡፡

በርግጥ ፕሮቴስታንት ለማንቋሸሽና ለማሳነስ የፈለጉት እ/ቅ/ድ ማርያምን ነው፡፡ ይሁን እንጂ በይበልጥ ያሳነሱት ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን እንደሆነ መረዳት ያስፈልጋል፡፡

ምክንያቱም በእነርሱ አባባል አንቺ ሴት ብሎ ማርያምን አዋርዷል ከተባለ ኢየሱስ ተሳዳቢና እናትና አባቱን የማያከብር እንኳን ለአምላክነት ቀርቶ ሥነ ምግባር ላለው ስብእና የማይበቃ ነው ያስብላል፡፡ ይህ ደግሞ ፈጽሞ ስህተት ነው፡፡

በዘጸ. 20 ላይ እናትህንና አባትህን አክብር ያለ እግዚአብሔር ወልድ ተመልሶ እናቱን አንቋሸሸ ብሎ መናገር ለሞራልም ለመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉምም የማይመች አባባል ነው፡፡ ከጌታ ኢየሱስ ንፁሐ ባህርይ ጋርም የማይሄድ ንግግር ነው፡፡

በሌላ መልኩ ደግሞ ልንሰደብ የሚገባንን እኛን ተቀብሎ ስለእኛ በአደባባይ ስድባችንን የተቀበለ አምላክ እናቱን ሰደበ ብሎ ማሰብ እብደት ነው፡፡ ስለዚህ ልናስተውል ይገባናል፡፡

ይቆየን

መ/ር ይቅርባይ እንዳለ

Read more http://eotcssd.org/dogma-ethiopian-orthodox-tewahedo-church/60-miscellaneous/386-2014-07-25-09-01-46.html