(ክፍል 1)

ይህን ቃል የጻፈልን ቅዱስ ሉቃስ ሲሆን ተናጋሪው ደግሞ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ነው።

የበራክዩ ልጅ ከሆነው ከካህኑ ዘካርያስና ከእናቱ ከቅድስት ኤልሳቤጥ የተገኘው ዮሐንስ መጥምቅ ካህኑ ዘካርያስ በእርጅና ሳለ፤ ቅድስት ኤላሳቤጥ ልምላሜ ጠፍቶባት በእርጅና ሳለች በእግዚአብሔር መልካም ፈቃድ በመልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ብሥራት እግዚአብሔርን በማምለክና በመፍራት ይኖሩ የነበሩ ካህኑ ዘካርያስ እና ኤልሳቤጥ እግዚአብሔርን እያገለገሉ ለዘመናት በኖሩበት መቅደስ የመልአኩን ብሥራት ካህኑ ዘካርያስ ሰማ "ልጅ ትወልዳለህ" የሚለውን የምሥራች ዜና።

      "ሁለቱም በእግዚአብሔር ፊት ፃድቃን ነበሩ" /ሉቃ፣ ፩፥፱/

ዮሐንስ ማለት ፍስሐ ወሐሴት ማለት ነው "በመወለዱም ብዙዎች ደስ ይላቸዋል" ሉቃ፣ ፩፥፲፬

ዮሐንስ መጥምቅ ክርስቶስን በ6 ወር በመወለድ ይቀድመዋል "እነሆ ዘመድሽ ኤልሳቤጥ እርሷ ደግሞ በእርጅናዋ ወንድ ልጅ ፀንሳለች ለእርሷም መካን ትባል ለነበረችው ይህ ስድስተኛ ወር ነው" ሉቃ፣ ፩፥፴፮  የጌታችንን መወለድ ንጉሡ ሄሮድስ በሰማበት ሰአት ክርስቶስን አገኛለሁ ብሎ ንጉሡ ከሁለት ዓመት በታች የሆኑትን ህፃናት አርዶ ደማቸው እንደ ውሃ በፈሰሰ ጊዜ /የህፃናቱ ብዛት 14እልፍ ከአራት ሺህ ናቸው/ የዮሐንስ እናት ቅድስት ኤልሳቤጥም ልጇን ይዛ በበረሃ ተሰዳ ነበረ እርሷም መስከረም ፯ ቀን በበረሃ አርፋለች። አባቱ ካህኑ ዘካርያስንም በቤተ መቅደስ ሄሮድስ ሰውቶታል። ዮሐንስም ለእስራኤል እስከሚገለጥ ድረስ ኑሮውን በብሕትውና፣ በትህርምት፣ በበረሃ በማድረግ ኖሯል። ጊዜው በደረሰ ጊዜ ግን ባማረና በተዋበ አለባበስ ሳይሆን የግመል ፀጉር ለብሶ፣ ወገቡን በጠፍር ታጥቆ፣ አንበጣና፣ የበረሃ ማር እየበላ በዮርዳኖስ ወንዝ የጌታን መንገድ አዘጋጁ ጥርጊያውንም አቅኑ እያለ ብርታትና ተግሳፅ በሞላበት አንደበት ማስተማር ጀመረ። ዮሐንስ ከልቡ አመንጭቶ የሚናገርበት ድፍረትና ጥብዓት ያገኘው በኖረው ፍፁም ብሕትውና እና የቅድስና  ኑሮ ነው "የእግዚአብሔርም ቃል ወደ ዘካርያስ ልጅ ወደ ዮሐንስ በምድረ በዳ መጣ"  ሉቃ፣ ፫፥፭ እንዳለ፦

ዮሐንስ ነቢይም፣ ካህንም፣ አጥማቂም፣ መምህርም፣ ጻድቅም፣ ሰማዕትም፣ ሐዋርያም ተብሎ ይጠራል።

 የጌታን መንገድ ለማዘጋጀት የዮሐንስ ትምህርቶች፣

  ፩/ ነስሑ እስመ ቀርበት መንግሥተ ሰማያት

  "መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ" ማቴ፣ ፫፥ ፩–፪

መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ የትምህርቱ መጀመሪያ፣ የመንገድ ጥርጊያው መጀመሪያ፣ ወደ እግዚአብሔር መመለሻው ንስሐ መጀመሪያው

ስለሆነ ተመለሱ ንስሐ ግቡ እያለ አስተማረ።

ንስሐ ማለት፦ መጸጸት፣ ማዘን፣ ማልቀስ፣ ክፉ ዐመልን መተው፣ መጥፎ ጠባይን መቀየር ማለት ነው። የብሉይ ኪዳን መጽሐፍ ሰፊውን ስፍራ የንስሐ ጥሪን መልእክት ይዞ እናገኛለን። በተለይ የነቢያት ጩኸት ወደ እግዚአብሔር ሕዝቡ እንዲመለስ፣ ከጣዖት አምልኮ እንዲርቅ፣ከዝሙት እንዲርቅ፣ ከሟርተኝነት እንዲርቅ፣ የሚያደርግ ድምጽ ነበር። እግዚአብሔርም ሰዎች ሲመለሱ የሚኖራቸው የሕይወት ለውጥ እንዲህ ብሎላቸዋል፦ "ኃጢአተኛውም ከሰራው ኃጢአት ሲመለስ ፍርድንና ቅን ነገርንም ቢያደርግ ነፍሱን ይጠብቃል አስቦ ከሰራው በደል ሁሉ ተመልሶአልና ፈጽሞ በህይወት ይኖራል እንጂ አይሞትም" ት/ሕዝ፣ ፲፰፥ ፳፯–፳፱

ቅዱስ ዮሐንስም ተመለሱና ንስሐ ግቡ የእግዚአብሔር መብግሥት ቀርባለችና እያለ ህዝቡን አስተምሯል። " ያን ጊዜም ኢየሩሳሌም ይሁዳም ሁሉ በዮርዳኖስም ዙሪያ ያለ አገር ሁሉ ወደ እርሱ ይወጡ ነበር ኃጢአታቸውንም እየተናዘዙ በዮርዳኖስ ወንዝ ከእርሱ ይጠመቁ ነበር" ማቴ፣ ፫፥ ፭–፮ እንዳለ።

በዮርዳኖስ ወንዝ የተሰበሰቡት ህዝብ ሁሉ የንስሐን ድምጽ ብቻ በመስማት አልዳኑም "ኃጢአታቸውንም ተናዘዙ" እንዳለ። ዛሬ ብዙዎቻችን የንስሐን ትምህርት የምናውቅ ግን ንስሐ የማንገባ፣ የምናዳምጥና የምንናገር ግን የማንተገብር፣ በከንፈራችን ብቻ የምንጸጸት እንጂ የሕይወት ለውጥ የማናመጣ ሆነናል። ንስሐ ኃጢአተኝነትን ብቻ ማመን አይደለም፣ ንስሐ የንስሐ እውቀትን ብቻ መያዝ አይደለም፣ ንስሐ ወደ እግዚአብሔር ቤት መምጣት ብቻ አይደለም፣ ንስሐ በልዩ ልዩ አገልግሎት ውስጥ መሰማራት ብቻ አይደለም፣ ንስሐ የሌሎችን ኃጢአት እያዩ የራስን አቅልሎ ማየት አይደለም፣ ንስሐ ኃጢአትንና የኃጢአትን ሰንኮፍ ነቅሎ ጥሎ ለአዲስ ሕይወት መኖር እንጂ፣ ንስሐ የእግዚአብሔርን የምሕረት አይን የምናይበት ልዩ መነጽራችን፣ የእግዚአብሔርን ይቅርታ የምናገኝበት ልዩ መንገዳችን፣ የእግዚአብሔርን ርኅራኄ የምናገኝበት ታላቁ ቀቁልፋችን ነው።

ለዚህ ነው መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ ያለው፤ ስለዚህ መልካም ወደ ሆነው ተመልሰን፣ የበደልን መልሰን፣ የተጣላን ታርቀን መኖር ያስፈልገናል።

የእውነት ሐዋርያ፣ የእውነት መስካሪና፣ ለእውነት የቆመ፣ ለእውነት የሄደ፣ መናኙ ካህን፣ የሰባኪው የመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ አማላጅነት ከሁላችን ጋር ይሁን።                                                                                

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፣ ወለወላዲቱ ድንግል፣ ወለመስቀሉ ክቡር!                                                                                                                  

መ/አ/ቀሲስ ስንታየሁ ደምስ

(- - - ይቀጥላል)